ጥምቀት

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

<<< በዓለ ኤጲፋንያ >>>

††† “ኤጲፋንያ” የሚለው ቃል ከግሪክ (ጽርዕ) ልሳን የተወሰደ ሲሆን በቁሙ “አስተርእዮ: መገለጥ” ተብሎ ይተረጐማል። በነገረ ድኅነት ምሥጢር ግን ኤጲፋንያ ማለት “የማይታይ መለኮት የታየበት: እሳተ መለኮት በተዋሐደው ሥጋ የተገለጠበት” እንደ ማለት ነው።

“ዘኢያስተርኢ ኅቡዕ እስመ አስተርአየ ለነ። እሳት በላዒ አምላክነ።” እንዲል። (አርኬ)

አንድም: ምሥጢር ሆኖ የቆየ አንድነቱ: ሦስትነቱ የተገለጠበት ቀን ነውና ዕለተ ጥምቀቱ ኤጲፋንያ ይሰኛል። መድኃኒታችን ክርስቶስ አዳምንና ልጆቹን ያድን ዘንድ ከሰማያት ዙፋኑ ወርዶ: እንደ ሰውነቱ በሥጋ ማርያም ለ33 ዓመታት ተመላልሷል። ጊዜው ሲደርስም በፈለገ ዮርዳኖስ: ከዮሐንስ ዘንድ ሊጠመቅ ሔደ። መድኃኒታችን ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ የወረደው ጥር 10 ቀን አመሻሽ ላይ ሲሆን በፍጹም ትሕትና ተራ ሲጠብቅ አድሮ ሌሊት 10 ሰዓት ላይ ደረሰውና ሊጠመቅ ቀረበ። አሥር ሰዓት መሆኑም ርግብ (መንፈስ ቅዱስ) ሲወርድ ሰዎች ሥጋዊት ርግብ ናት ብለው እንዳይጠራጠሩ ነው። ርግብ በሌሊት መንቀሳቀስ አትችልምና። መድኃኒታችን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ሲጠጋ አምላክነቱን ተረድቶ “እንዴት ፈጣሪየ ወደ እኔ ትመጣለህ? እንዴትስ በእኔ እጅ ትጠመቃለህ?” አለው። ትህትና ለእናትና ልጅ ልማዳቸው ነውና። ጌታ ግን “ጽድቅን ሁሉ ልንፈጽም ይገባል” ሲል እንዲያጠምቀው ፈቀደለት። ቅዱስ ዮሐንስም “ስመ አብ በአንተ ሕልው ነው። ስመ ወልድ ያንተ ነው። ስመ መንፈስ ቅዱስም በአንተ ዘንድ ሕልው ነው። በማን ስም አጠምቅሃለሁ?” ሲል ጠየቀው። ጌታ “ወልዱ ለቡሩክ ከሣቴ ብርሃን ተሣሐለነ። አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሲመቱ ለመልከ ጼዴቅ” እያልክ አጥምቀኝ አለው። ትርጉሙም “የቡሩክ አብ የባሕርይ ልጁ : ብርሃንን የምትገልጥ ሆይ ይቅር በለን! አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዓለም ካህኑ ነህና” እንደ ማለት ነው። ከዚያም ጌታ ወደ ዮርዳኖስ ሲገባ ባሕር አይታ ደነገጠች : ሸሸችም። (መዝ. 76:16, 113:3) ዮርዳኖስ ጨንቆት ግራ ቀኝ ተመላለሰ። እሳተ መለኮት ቆሞበታልና ውኃው ፈላ። በጌታ ትዕዛዝ ግን ጸና። ጌታ ተጠምቆ: ሥርዓተ ጥምቀትን ሠርቶ: ዮርዳኖስን ብርህት ማሕጸን አድርጐ: የእዳ ደብዳቤአችንንም ቀዶ ከወጣ በኋላ ሰማያት ተከፈቱ። ማለትም አዲስ ምሥጢር ተገለጠ። አብ በደመና ሆኖ “የምወደው: የምወልደው: ሕልው ሆኜ ልመለክበት የመረጥኩት የባሕርይ ልጄ ይህ ነው!” ሲል በአካላዊ ቃሉ ፍጹም ተዋሕዶን መሰከረ። መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ ወርዶ በራሱ ላይ ተቀመጠ። ራሱንም ቆንጠጥ አድርጐ ያዘው። በዚህም የሥላሴ አንድነቱ: ሦስትነቱ ታወቀ: ተገለጠ። ቅዱስ ዮሐንስ “መጥምቀ መለኮት” የሚባልበትን ታላቁን ክብር ሲያገኝ ዮርዳኖስ የልጅነት መገኛ ቅዱስ ባሕር ሆነ።

<<< ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ >>>

ቅዱስ ወንጌል ላይ ቅዱስ ሉቃስ “ዘካርያስ ካህኑና ቅድስት ኤልሳቤጥ በሰውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ የሚኖሩ ጻድቃን ነበሩ” ይላቸዋል። (ሉቃ. 1:6) እሊህ ቅዱሳን ባልና ሚስት ግን መካኖች በመሆናቸው ልጅ ሳይወልዱ ዘመናቸው አልፎ ነበር። እንደ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ዕድሜአቸው የኤልሳቤጥ 90 የዘካርያስ ደግሞ 100 ደርሶ ነበር። ፍጹም መታገሳቸውን የተመለከተ ጌታ ግን በስተ እርጅናቸው ከሰው ሁሉ በላይ የሆነ: ትንቢት ለብቻው የተነገረለት (ኢሳ. 40:3, ሚል. 3:1) ታላቅ ነቢይን ይሰጣቸው ዘንድ መልአከ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤልን ላከላቸው። ቅዱስ ዘካርያስ ሰው ነውና ከደስታ ብዛት በመከራከሩ ድዳ ሆነ። ቅድስቲቷ ግን መስከረም 26 ቀን ታላቁን ሰው ጸንሳ ለ6 ወራት ራሷን ሠወረች። በ6ኛው ወር የፍጥረት ሁሉ ጌታ በተጸነሰ ጊዜ የአርያም ንግሥት ድንግል እመቤታችን ደጋ ደጋውን ወደ ኤልሳቤጥ መጣች። ሁለቱ ቅዱሳት የእህትማማች ልጆች ናቸው። የአምላክ እናቱ ስትደርስና “ሰላም” ስትላቸው መንፈስ ቅዱስ በእናትና ልጅ ወርዶ ኤልሳቤጥ በምስጋና: ዮሐንስ ደግሞ ገና በማሕጸን ሳለ በደስታ ዘለለ (ሰገደ)። ከዚህ በኋላ ሰኔ 30 ተወልዶ: አባቱ ዘካርያስ “ዮሐንስ” ሲለው አንደበቱ ተፈትቶለታል።

ቅዱስ ዮሐንስ ከተወለደ 2 ዓመት ከ6 ወር በሆነው ጊዜ ሰብአ ሰገል በመምጣታቸው በእሥራኤል ምድር የሚገኙ ሕፃናትን ሔሮድስ ቁዝ አስፈጀ። ትንሽ ቆይቶም አይሁድ ለሔሮድስ ስለ ቅዱሱ ሕፃን ነገሩት። “ሲጸነስ የአባቱን አንደበት የዘጋ: ሲወለድ ደግሞ የከፈተ ‘ዮሐንስ’ የሚባል ሕፃን አለና እሱንም ግደል” አሉ። እናቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ ይዛው ስትሸሽ ካህኑን ዘካርያስን ግን በቤተ መቅደስ መካከል ገድለውታል። አረጋይት ኤልሳቤጥም ሕፃኑን እያሳደገች በገዳመ ዚፋታ ለ3 (5) ዓመታት ቆይታለች። ቅዱስ ዮሐንስ 5 (7) ዓመት ሲሞላው ግን እዚያው በበርሃ እናቱ ዐረፈች። ከሰማይ ዘካርያስና ስምዖን ወርደው ቀበሯት። ሕፃኑ ዮሐንስ ሲያለቅስ ድንግል ማርያም ስንት አገር አልፋ ሰማችው። እርሷም ስደት ላይ ነበረችና። ከጌታ ጋር በደመና ሒደው ድንግል አቅፋ አጽናናችው። ጌታንም “እንውሰደው ይሆን?” አለችው። ጌታችን ግን “ለአገልግሎት እስክጠራው እዚህ ይቆይ” አላት። ባርካው: አጽናንታውም ተለያዩ። ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ በኋላ በዚያ ቆላ የግመል ጠጉር ለብሶ: ጠፍር ታጥቆ ተባሕትዎውን ቀጠለ። ለ25 (23) ዓመታትም በንጽሕና ሲኖር ከምድር አራዊትና ከሰማይ መላእክት በቀር ማንንም አላየም። ይሕችን ዐመጸኛ ዓለምም አልቀመሳትም።

ከዚህ በኋላ 30 ዘመን ሲሞላው እግዚአብሔር ከሰማይ ተናገረው። “ሒድ! የልጄን ጐዳና ጥረግ” አለው። ነቢያት ስለዚህ ነገር ተናግረው ነበርና። (ኢሳ. 40:3, ሚል. 3:1) አባቱ ዘካርያስም “ወአንተኒ ሕፃን ነቢየ ልዑል ትሰመይ: እስመ ተሐውር ቅድመ እግዚአብሔር ከመ ትጺሕ ፍኖቶ” (ሉቃ. 1:76) ብሎ መንገድ ጠራጊነቱን ተናግሮ ነበርና። ቅዱስ ዮሐንስ በዚያ ጊዜ በኃይለ መንፈስ ቅዱስ እየገሰገሰ ከበርሃ ወደ ይሁዳ መጣ። ያዩት ሁሉ ፈሩት: አከበሩት። ቁመቱ ቀጥ ያለ: ጽሕሙ እንደ ተፈተለ ሐር የወረደ: ጸጉሩ የቁራ ያህል የጠቆረ: መልኩ የተሟላ: ግርማው የሚያስፈራ ገዳማዊ ነውና። ፈጥኖም ሕዝቡን ለንስሐ ሰበከ: ለንስሐም በርካቶችን አጠመቃቸው። በዚህ አገልግሎት ለ6 ወራት ቆይቶ ጌታችን ወደ እርሱ ዘንድ መጣ። ዮሐንስ ሰማይን ከነግሱ: ምድርን ከነልብሱ የያዘ ፈጣሪ “አጥምቀኝ” ብሎ ሲመጣ ደነገጠ። የሚገባበትም ጠፋው። “እንቢ ጌታየ! አንተ አጥምቀኝ” አለው። ጌታ ግን “ፈቅጄልሃለሁ” አለው: አጠመቀው። በዚህ ምክንያት ይሔው እስከ ዛሬም “መጥምቀ መለኮት” ሲባል ይኖራል። ቅዱስ ዮሐንስ በመጨረሻ ሔሮድስን ገሰጸው። ንጉሡም ተቀይሞ ለ7 ቀናት አሠረው። ልደቱን ባከበረ ጊዜ ወለተ ሔሮድያዳ በዘፈን አጥምዳ አስማለችው። እርሱም የታላቁን ነቢይ ራስ አስቆርጦ በወጪት አድርጐ ሰጣት። አበው “እምሔሶ ለሔሮድስ ይብላዕ መሐላሁ – ሔሮድስ መሐላውን በበላ በተሻለው ነበር” ይላሉ። የቅዱስ ዮሐንስ ራሱ በርራ ስትሔድ አካሉን ግን ደቀ መዛሙርቱ ቀብረውታል። (ማቴ. 3:1, ማር. 6:14, ሉቃ. 3:1, ዮሐ. 1:6)

=>”አስማተ-ዮሐንስ መጥምቅ /የመጥምቁ ዮሐንስ ስሞች”

  1. ነቢይ
  2. ሐዋርያ
  3. ሰማዕት
  4. ጻድቅ
  5. ካሕን
  6. ባሕታዊ / ገዳማዊ
  7. መጥምቀ መለኮት
  8. ጸያሔ ፍኖት (መንገድ ጠራጊ)
  9. ድንግል
  10. ተንከተም (የብሉይና የሐዲስ መገናኛ ድልድይ)
  11. ቃለ አዋዲ (አዋጅ ነጋሪ)
  12. መምሕር ወመገሥጽ
  13. ዘየዐቢ እምኩሉ (ከሁሉ የሚበልጥ)

=>አምላከ ቅዱሳን በጥምቀቱ ይቀድሰን። ከበረከተ ጥምቀቱም ያድለን።

=>ጥር 11 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ በዓላት

  1. በዓለ ኤጲፋንያ
  2. ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ
  3. አቡነ ሐራ ድንግል ጻድቅ
  4. አባ ወቅሪስ ገዳማዊ
  5. አባ ዮሐንስ ሊቀ ጳጳሳት
  6. ቅዱስ እንጣልዮስ ሰማዕት

=>ወርኀዊ በዓላት

  1. ቅዱስ ያሬድ ካህን
  2. ማር ገላውዴዎስ ሰማዕት
  3. ቅዱስ ፋሲለደስ ሰማዕት
  4. ቅድስት ሐና ቡርክት

=>”ጌታ ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያው ከውኃ ወጣ። እነሆም ሰማያት ተከፈቱ። የእግዚአብሔርም መንፈስ እንደ ርግብ ሲወርድ: በእርሱ ላይም ሲመጣ አየ። እነሆም ድምጽ ከሰማያት መጥቶ:- ‘በእርሱ ደስ የሚለኝ: የምወደው ልጄ ይህ ነው’ አለ።” (ማቴ. ፫፥፲፮)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ከዲ/ን ዮርዳኖስ ማስታወሻ